የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ከዚህ በፊት ከነበረው አሠራር ለየት ያሉ ተግባራት እንደሚከወኑ ተገለፀ።

(መስከረም 12፣ 2013 ዓ.ም) የከፍተኛ ትምህርትና ስልጠናን ለማስቀጠል ቅድመ ዝግጅትና የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ምላሽ ተግባራት አፈፃፀም የግምገማ መድረክ በትምህርት ዘርፍ ሪፎርም ላይ ትኩረቱን አድርጎ ዛሬም ቀጥሏል።

የሪፎርሙ አካል የሆነው የትምህርት ጥራትን የማረጋገጥ ተግባርን ከግብ ለማድረስ ከየትምህርት ተቋማቱ ጠንካራ የአይ.ሲ.ቲ ባለሙያዎች ተመርጠው በሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ማዕከልነት የትምህርት ስርዓት መረጃን በማደራጀት የመረጃ ልውውጥን ለማዘመን ይሰራል ተብሏል።

የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትሩ ዶ/ር ሳሙኤል ኡርካቶ እንደተናገሩት ለምርምር; ለአፕላይድ እና ኮምፕሪሄንሲቭ ዩኒቨርሲቲነት የተመረጡ ዩኒቨርሲቲዎች የተቋቋሙለትን አላማ ከግብ ለማድረስ ይሰራሉ ብለዋል።

ለረጅም ግዜ የቅሬታ መንስዔ የሆኑት ጥናታዊ ጽሁፎች ከመደርደሪያ ወርደው ለማህብረሠቡ ጥቅም በመስጠት አለም አቀፍ የትምህርት ገበያውን መቀላቀል እንዲችሉ ማድረግ እና በሀገር በቀል እውቀት የታገዘ ትምህርት መስጠት የሚያግዝ የሪፎርም ስራ እንደሚሰራ ተወስቷል።

ይህንን ተግባር ከግብ ለማድረስ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር 95% የአቅም ግንባታ እንዲሁም 5% የሬጉሌሽን ስራዎች እንደሚሰራ ሚኑስትሩ ዶ/ር ሳሙኤል ኡርካቶ ገልፀዋል።

የትምህርት ጥራት; ተደራሽነትና ፍትሃዊነትን ለማረጋገጥ የክትትልና ምዘና ስራ በስፋት የሚሰራ ሲሆን ተግባሩም የሚከናወነው በሀገር አቀፍ ደረጃ በሚቋቋም ሃላፊነት ያለው ተቋም ይሆናል።

ምሩቃንን; የመምህራን ብቃትን; የምርምር ጥራትንና የካሬኩለም ጥራትን የመመዘን ስራን ይኸዉ ተቋም ያከናውናል ተብሏል።

ከዚህ ቀደም ዩኒቨርስቲዎች የመመዝን ተግባርን ያከናውኑ ነበር።

የከፍተኛ ትምህርትና ስልጠናን ለማስቀጠል ቅድመ ዝግጅትና የኮቪድ-19 ወረርቭኝ ምላሽ ተግባራት አፈፃፀም የግምገማ መድረክ ቀጥሎ በአሁኑ ሠዓት የገበታ ለሀገር መርሃ-ግብር ላይ በመወያየት ላይ ይገኛል፡፡