የግቢ ጽዳትና ውበት ንቅናቄ በጅማ ዩኒቨርሲቲ

ተማሪዎችን የመቀበል ሂደት አካል የሆነው የግቢ ጽዳትና ውበት ንቅናቄ ተካሂዷል።

ጅማ ዩኒቨርሲቲ በተያዘው አመት ሁለንተናዊ የግቢ ጽዳትና ውበት ለውጥ ለማምጣት አቅጣጫ አስቀምጦ የንቅናቄ መርሃ-ግብር አዘጋጅቶ ወደ ስራ መግባቱ ታውቋል።

ጅማ ዩኒቨርሲቲ በዋናው ግቢ፣ በቢዝነስና ኢኮኖሚክስ፣ በግብርናና እንስሳት ህክምና ኮሌጅ እንዲሁም በቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የጽዳትና ውበት ስራን በዛሬው እለት ሲያከናውን ውሏል።

የተማሪዎች መኝታ፣ መመገቢያ፣ መማሪያ እና መዝናኛ እንዲሁም ሌሎች የየካምፓሶቹ ስፍራዎች የተፀዱ ሲሆን ይህም ተማሪዎች ወደ ዩኒቨርሲቲው ሲመጡ መንፈስን የሚያድስ ማራኪ ገፅታ እንዲኖራቸው ያስችላል ተብሏል።

ንቅናቄውን በዩኒቨርሲቲው አስተዳደርና ተማሪዎች አገልግሎት ም/ ፕሬዚደንት ስር የሚገኙ የጠቅላላ አገልግሎት፣ የተማሪዎች አገልግሎት፣ የግቢ ውበት ሠራተኞች እና ሁሉም የፅዳት ሠራተኞች አከናውነዋል።

ምቹ፣ ጽዱና ሠላማዊ የመማር ማስተማር ሂደትን ለመፍጠር በሚደረገው ንቅናቄ ተሳታፊ ለሆኑ ሠራተኞች ዩኒቨርሲቲው ምስጋና ያቀረበ ሲሆን ሂደቱ ቀጣይነት እንዲኖረው ለማድረግ ሁሉም በሀሳብ፣ በጉልበትና በሌሎች ተግባራትም እንዲያግዙ ጥሪ ቀርቧል።