ለሴት አካዳሚክ አባላት ስልጠና እየተሰጠ ነዉ፡፡

Network for Advancement of Sustainable Capacity in Education and Research in Ethiopia (NASCERE) ፕሮግራም ለ15 ቀናት በሚሰጠዉ የአቅም ማጎልበት ስለጠና ላይ ከ35 በላይ ሴት መምህራን በመሳተፍ ላይ ናቸዉ፡፡
የጅማ ዩኒቨርሲቲ አካዳሚክ ም/ፕሬዝደንት ዶ/ር ታደሰ ሀብታሙ ጥቂት ፒ.ኤች.ዲ የያዙ ሴት መምህራን ባሉበት; አገራዊ ሁኔታ የስልጠናው ተሳታፊዎች ይህንን እድል በመጠቀም ለዉጥ የሚያመጣ ገዢ ሃሳብ አፍልቀዉ ራሳቸዉን ለስኬት ሊያበቁ እንደሚገባና ለዚህም ስኬት ጠንክረዉ ሊሰሩ እንደሚገባ በስልጠናዉ መክፈቻ ላይ ተናግረዋል፡፡
ከአቅም ማጎልበት ስልጠናዉ ጎን ለጎን ሰልጣኞች ኮንሰፕት ኖት (concept note) በማዘጋጀት ለሶስተኛ ዲግሪ ትምህርት ዉድድር ራሳቸዉን እያዘጋጁ እንደሚሄዱ የተገለፀ ሲሆን የሚያዘጋጁት ኮንሰፕት ኖትም ቤልጄም ሀገር ወደሚገኙት ዩኒቨርሲቲዎች ተልከዉ ለዉድድር ይቀርባሉ እድለኞችም ተጠቃሚ ይሆናሉ ተብሏል፡፡
በጅማ ዩኒቨርሲቲ የቢዝነስና ዴቨሎፕመንት ም/ፕሬዚደንት እና NASCERE ፕሮጀከት አስተባባሪ አቶ ኮራ ጡሹኔ እንደገለፁት ከሀገራችን ህዝብ ግማሽ የሚሆኑት ሴቶች ሲሆኑ በሶስተኛ ዲግሪ ደረጃ ያሉት ቁጥራቸዉ እጅግ ዝቅተኛ ነዉ፡፡ የሴቶች ተሳትፎ የሀገር እድግት ማሳያ ነዉ ያሉት አቶ ኮራ ይህ ስልጠና የሴቶችን ተሳትፎ በማሳደግ በዩኒቨርሲቲያችን የሚስተዋለዉን የሴት ፒ.ኤች.ዲ ባለቤቶች እጥረት እንደሚቀርፍ ገልፀዋል፡፡
በዩኒቨርሲቲዉ…የአካዳሚክ ጉዳዮች ም/ፕሬዝዳንት አማካሪ የሆኑት ዶ/ር ማኑኤል ኦሉ ጅማ ዩኒቨርሲቲ ወደ ምርምር ዩኒቨርሲቲነት የሚያደርገዉን ጉዞ ከማሳለጥ አንፃር ይህ ስልጠና ሚናዉ ከፍተኛ ነዉ ብለዋል፡፡
የአቅም ማጎልበቻ ስልጠናዉ በጅማ ዩኒቨርሲቲ በሚገኙ ምሁራን እየተሰጠ ለ15 ቀናት የሚቀጥል ነዉ፡፡